وَمَا لَكُمْ لَا تُقَـٰتِلُونَ فِى سَبِيلِ ٱللَّهِ وَٱلْمُسْتَضْعَفِينَ مِنَ ٱلرِّجَالِ وَٱلنِّسَآءِ وَٱلْوِلْدَٰنِ ٱلَّذِينَ يَقُولُونَ رَبَّنَآ أَخْرِجْنَا مِنْ هَـٰذِهِ ٱلْقَرْيَةِ ٱلظَّالِمِ أَهْلُهَا وَٱجْعَل لَّنَا مِن لَّدُنكَ وَلِيًّۭا وَٱجْعَل لَّنَا مِن لَّدُنكَ نَصِيرًا
በአላህ መንገድና ከወንዶች፣ ከሴቶችና ከልጆችም የኾኑትን ደካሞች እነዚያን፦ “ጌታችን ሆይ! ከዚች ባለቤቶችዋ በዳይ ከኾኑት ከተማ አውጣን፤ ከአንተም ዘንድ ለኛ አሳዳሪ አድርግልን፤ ከአንተ ዘንድም ለኛ ረዳትን አድርግልን።” የሚሉትን (ለማዳን) የማትጋደሉት ለእናንተ ምን አላችሁ? (ሱረቱ አል-ኒሳእ:75)
በቃ ማለታችን አልበቃም፤ እንደገና ተደገመ
እኛ በቴክሳስ ዳላስ ፎርት ዎርዝ አካባቢ የምንኖር ሙስሊም ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ-ኢትዮጵያውያን ከሰሞኑ በአማራ ክልል በተለይም በጎንደር ከተማ ውስጥ በሚኖሩ ሙስሊሞች ላይ በአክራሪ ኦርቶዶክሳዊያን የተፈፀመውን አረመኔያዊ ጭፍጨፋ ድብደባ ዘረፋና ስቃይ እጅግ በመረረ መልኩ እናወግዛለን።
በተለይም ካሁን በፊት በአማራ ክልል በሞጣና ሌሎች ከተሞች ላይ አሁን ደግሞ በጎንደር ከተማና ባካባቢው በሙስሊም ኢትዮጵያውያን ላይ እንስሳዊ ድርጊት የፈጸሙ ሰዎችን እንደተለመደው በቸልተኝነት በመመልከት ለዚህ አሳፋሪ ድርጊት ቅድመ ሁኔታዎችን ያመቻቹትን የአማራ ክልል አስተዳደርና የፀጥታ ኣካላት በከፍተኛ ቁጣ እናወግዛቸዋለን። በአላህ(ሱወ) ፍቃድም ካሁን በፊት እንደነበሩት በደለኞች በተቻለው መልኩ ሁሉ ለፍርድ እንዲቀርቡ እንጥራለን።
ዛሬም ድረስ በህይወት ያሉ ሰዎች የሚመሰክሩትና በመረጃ የተደገፈ ታሪክ በግልፅ እንደሚያሳየው ሙስሊም አትዮጵያውያን ካሁን በፊት በነበሩ መንግስታትና መሪዎች የተለያዩ ገፅታ ያላቸው ግልፅና ድብቅ ግፍና በደል ይደርስባቸው እንደነበር ይታወቃል። ከነዚህም ውስጥ ሙስሊሞችን በጅምላ መግደል፣ ሃይማኖታቸውን እንዲቀይሩ ማስገደድ፣ በተወለዱባት ሃገራቸው ውስጥ እንደ ሁለተኛ ዜጋ በመፈረጅ ሃይማኖታቸውን ፈጣሪ ባዘዘው መልኩ እንዳይተገብሩ በማድረግ፣ የሙስሊም ኢትዮጵያውያንን ታሪክ በመካድ፣ በማጠልሸትና በመከለስ ለምዕተ ዘመናት የዘለቁት ግፎች በሃገሪቱ ላይ መቼም የማይረሱና የማይጠፉ አሳፋሪ የታሪክ አሻራዎች ናቸው።
አሁንም ይህንን አሳፋሪ ታሪክ የማስቀጠል እኩይ አላማቸውን በማባባስ በጎንደር ከተማ እንደተደረግው አብረው ተወልደው አብረው የኖሩ ሙስሊም ኢትዮጵያውያንን በጅምላ በመግደል ከተወለዱበት መሬት በማፈናቀል መስጊዶችን በማውደምና የለፉበትን ንብረታቸውን በመዝረፍ ስብዕና ፈጽሞ የጠፋበትን እንስሳዊ ድርጊታቸውን በማናለብነኝት አጠናክረው መቀጠላችው በማንኛውም ቦታ ያለን ሙስሊም ኢትዮጵያውያን ላይ ከፍተኛ ቁጣ ቀስቅሶብናል።
በዚህም የተነሳ እኛ በቴክሳስ ዳላስ ፎርት ዎርዝ አካባቢ የምንኖር ሙስሊም ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ-ኢትዮጵያውያን፦
- በጎንደር ከተማ ሙስሊም ኢትዮጵያውያንን በጅምላ የመግደል ከተወለዱበት መሬት የማፈናቀል መስጊዶችን የማውደምና የለፉበትን ንብረታቸውን የመዝረፍ አረመኔያዊ ድርጊቶችን በከፍተኛ ድምፅ እናወግዛለን፤
- የፌደራልና የክልል መንግስት አካላት እነዚህን እኩይ ተግባራትን የፈፀሙትን አረመኔ ወንጀለኞች፣ ከጀርባ በመሆንም እንደዚህ አስፀያፊ ድርጊቶችን ያቀነባበሩትን መሰሪ አሸባሪዎች በፍጥነት ለፍርድ እንዲያቀርቡ አበክረን እንጠይቃለን፤
- የፌደራልና የክልል መንግስት አካላት ለጠቅላላው የሃገሩቱ ህዝብ ያለባቸውን ሃላፊነት ከማንኛውም የዘር የሃይማኖትና የጎሳ አድልዎ በፀዳ መልኩ እንዲወጡ ይህንንም ከወገንተኝነት ነፃ የሆነ አስተዳደራዊ ስራ የሚያውኩ በየደረጃው የተሰገሰጉ ሃላፊዎችና አማካሪዎች ላይ አስቸኳይ የማስተካከያ እርምጃዎች እንዲወስዱ አበክረን እንጠይቃለን፤
- ካሁን በፊት እጅግ በጣም ብዙ መስጊዶች ሲቃጠሉ በቸልተኝነት የተመለከተው የአማራ ክልል መንግስት አሁን ህይወታችውን በግፍ እስከማጣት የደረሱ የአሸባሪ ኦርቶዶክሳዊያን ጥቃት ሰለባዎችና ሙስሊም ኢትዮጵያውያንን ይቅርታ እንዲጠይቅ ለተጎዱ ሰዎችም ተገቢውን ካሳ እንዲከፍል እንዲሁም የተቃጠሉና የፈረሱ የሃይማኖት ተቛማትን በራሱ ወጪ በተቻለ ፍጥነት መልሶ እንዲያሰራ እንጠይቃለን፤
- እንዲህ ኣይነት አሳፋሪ ድርጊቶች ዳግም እንዳይፈፀሙ የሚመለከታቸው የፌደራልና የክልል መንግስትና የፀጥታ አካላት ለሁሉም ኢትዮጵያውያንና የሃይማኖት ተቛማት እኩልና ዘላቂ ጥበቃ እንዲያደርጉ እንጠይቃለን።
ሙስሊም ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ-ኢትዮጵያውያን ለሃገራችን ያለን ጥልቅ ውዴታ ምንጩ መሬቱና ተራራው ሳይሆን እስልምና መሆኑን ማንም ሰው ሊያውቀው ይገባል። እኛ ለሃገራችን ስንለፋና ስንሰዋ እስልምና ለሃይማኖታችን፣ ለራሳችን፣ ለቤተሰባችን፣ ለጎረቤቶቻችን፣ ለዘመዶቻችን፣ ለንብረታችንና ለሃገራችን አስፈላጊውን ሁሉ መስዋእትነት እንድንከፍል ስለሚያዘን ነው። አላህ (ሱወ) በቁርአን ውስጥ እንዳዘዘን ስግደታችንም መገዛታችንም መኖራችንም ሆነ መሞታችን ለአለማት ጌታ አላህ (ሱወ) ብቻ መሆኑን ማንኛውም በእስልምና ላይ የተሳሳተ አመለካከት ያለው ሰው ጠንቅቆ ቢያውቅና ሁሌም ቢያስታውስ ይበጀዋል። ሙስሊም ኢትዮጵያውያን እጅግ በጣም ታጋሾችና በፈጣሪያችን ብቻ የምንመካ ብንሆንም በደል ሲበዛብን በተለይ በሃይማኖታችን በመጡ ጉዳዮች ላይ በፍፁም የማንደራደርና ካሁን በፊት የነበሩትን ጨቛኝና በዳይ ሥርዓቶችን የገረሰሱ አንፀባራቂ ትግሎች ጀማሪና ዋነኛ አካል እንደነበርን ሁሌም ማስታወስ ይገባል።
አላህ (ሱወ) ህዝባችንና ሃገራችንን እንዲጠብቅልን እንለምነዋለን። በየትኛውም ስፍራ የምንኖር ኢትዮጵያውያን በጋራ በመሆን ሃገራችንን ወደ ብጥብጥና እርስ በርስ መተላለቅ እንድንገባ በግልፅና በስውር የሚንቀሳቀሱ መሰሪ አካላትን ሴራ ለማክሸፍ አስፈላጊውን ርብርብና ያላሰለሰ ጥረት እንድናደርግ በፈጣሪያችን ስም ጥሪ እናቀርባለን።
ቢላል ኮሚኒቲ ሴንተር
ዳላስ-ፎርት ዎርዝ, ቴክሳስ
May 1, 2022